የሰባት ወር ፍልስጤማዊ ጨቅላ በእስራኤል ጥቃት መገደሉ ተገለጸ

የፎቶው ባለመብት, Reuters
በይዞታ ሥር ባለችው ዌስት ባንክ የሰባት ወር ፍልስጤማዊ ጨቅላ በእስራኤል ጥቃት መገደሉን የፍልስጤም የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።
በሄብሮን ከተማ፣ ታል ሩሚዳ አካባቢ ሳም ፋሐድ አቡ ሐኪል የተባለው ጨቅላ ወላጆችም ከእስራኤል በተተኮሰ ጥይት ጉዳት ደርሶባቸዋል።
የእስራኤል መከላከያ ኃይል አርብ ዕለት ወታደሮቹ “ወደ እነሱ እየገሰገሰ የሚሄድ መኪና እንደተመለከቱ” ገልጾ ከወታደሮቹ አንደኛው “አንድ ጥይት ወደ ተሽከርካሪው በመተኮስ ምላሽ መስጠቱን” ገልጿል።
“በዚህም ምክንያት ሦስት ፍልስጤማውያን ተጎድተው ወደ ሕክምና ተወስደዋል። ክስተቱ ላይ ምርመራ እየተደረገ ነው። የማይመለከታቸው ሰዎች በመጎዳታቸው ጥልቅ ሐዘን ተሰምቶናል” ሲልም ጦሩ አስታውቋል።
ቤተሰቡ የእስራኤልን ወታደራዊ ተሽከርካሪ ከሩቅ ሲመለከት መኪናውን ማቆሙን የጨቅላው አያት መናገራቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።
ከዚያም ወደ መኪናቸው ሲተኮስ ማስጠንቀቂያ እንደመሰላቸው አያትየው ተናግረዋል።
“አንድ ጥይት የልጅ ልጄን መታው። ጥይቱ ጭንቅላቱን ሲመታው የልጄን ጉንጭም ጭሯት አልፏል” ብለዋል።





















