አሜሪካ እና ኢራን በባሕረ ሰላጤው አካባቢ የተኩስ ልውውጥ አደረጉ

የፎቶው ባለመብት, AFP
የአሜሪካ ጦር ኢራን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ የተኮሰቻቸውን አራት ድሮኖች መትቶ መጣሉን አስታወቀ።
“አንድ ጊዜ ብቻ ጥቃት የሚያደርሱት ድሮኖች በባሕር እንቅስቃሴ ላይ አደጋ ጥለዋል” ሲል ጦሩ ገልጿል።
የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ፤ ጎሩክ እና ቃሽም በተባሉ ደሴቶች ላይ የኢራን የባሕር ዳርቻ ጥበቃ ማዕከላት ላይ ጥቃት መፈጸሙን ጠቅሷል።
ኢራንም በአጸፋው በኩዌት የሚገኙ ሁለት የአሜሪካ ጦር መቀመጫዎች ላይ ባለስቲክ ሚሳዔል ተኩሳለች። በባሕሬን በሚገኘው የአሜሪካ ጦር ሰፈር ላይም ጥቃት ማድረሷን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ እንዳለው ከባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ኢራን ከተኮሰቻቸው ሰባት ሚሳዔሎች ስድስቱ ዒላማቸውን ሳይመቱ ማክሸፍ ተችሏል።
በተደጋጋሚ በሚፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት የኢራን እና የአሜሪካ የተኩስ አቁም ስምምነት አደጋ ውስጥ ወድቋል።
ከቀናት በፊትም ተመሳሳይ የተኩስ ልውውጥ ተደርጎ እንደነበር ይታወሳል።
ኢራን በኩዌት ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በፈጸመችው የድሮን ጥቃት አንድ ሰው ሲገደል፤ 60 ሰዎች ቆስለዋል።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በአውሮፕላን ማረፊያው ጥቃት መፈጸሙን አስተባብሏል። ጉዳት የደረሰው በተሳሳተ የአሜሪካ ሚሳዔል አምካኝ ምክንያት መሆኑንም ገልጿል።






















