ቀጥታ, ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ወደ ፓኪስታን የሚያደርጉትን ጉዞ መሰረዛቸውን ተናገሩ

ዶናልድ ትራምፕ ለፎክስ ኒውስ የስቲቭ ዊትኮፍን እና ጃሬድ ኩሽነር የፓኪስታን ጉዞ መሰረዛቸውን ተናገሩ። ፕሬዚዳንት ትራምፕ “ሁሉም ዕድል በእጃችን ነው። በፈለጉ በማንኛውም ጊዜ ሊደውሉልን ይችላሉ፤ ነገር ግን ምንም ላለመነጋገር ከ18 ሰዓታት በላይ ጉዞ ማድረግ የለባቸውም” ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ወደ ፓኪስታን የሚያደርጉትን ጉዞ ሰረዙ

    ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    ዶናልድ ትራምፕ ለፎክስ ኒውስ ልዩ መልዕክተኛው ስቲቭ ዊትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነር ወደ ፓኪስታን ለውይይት እንደማይሄዱ ተናገሩ።

    ፕሬዚዳንቱ "ሁሉም አማራጮች አሉን፤ በፈለጉት ጊዜ ሊደውሉልን ይችላሉ፤ ነገር ግን ምንም ነገር ላለመነጋገር ተጨማሪ የ18 ሰዓት በረራ አያደርጉም።" ብለዋል።

    የፎክስ ኒውስ የዋይት ሐውስ ዘጋቢ ፕሬዚዳንት ትራምፕ "ሰዎቼን ነገርያቸዋለሁ፤ ከጥቂት ሰዓት በፊት ለመሄድ እየተዘጋጁ ነበር እና 'አይሆንም ወደዚያ ለመሄድ የ18 ሰዓት በረራ አታደርጉም' ብያቸዋለሁ” ማለታቸውን ጠቅሷል።

    ትራምፕ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ የልዑካን ቡድኑን ጉዞ መሰረዛቸውን አረጋግጠዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት የአሜሪካ ልዑካን ወደ ኢዝላማባድ የሚያደርጉትን ጉዞ የሰረዙት ”በጉዞ ብዙ ሰዓት ነው የሚጠፋው፤ ብዙ ሥራ ነው” በማለት ነው።

    “ወኪሎቼ ወደ ፓኪስታን ኢዝላማባድ ኢራናውያንን ለማግኘት የሚያደርጉትን ጉዞ ሰርዣለሁ።”

    “ከዚህም በተጨማሪ በአመራሩ መካከል ከፍተኛ ክፍፍል እና ግራ መጋባት አለ። ማንም መሪው ማን እንደሆነ አያውቅም። እነርሱን ጨምሮ።

    በተጨማሪም ሁሉም አማራጭ አለን። እነርሱ ግን ምንም የላቸውም! መነጋገር ከፈለጉ ማድረግ ያለባቸው መደወል ብቻ ነው!!!’’ ብለዋል

  2. ወደ ፓኪስታን የሚጓዙት የትራምፕ ተደራዳሪዎች ጃሬድ ኩሽነር እና ስቲቭ ዋትኮፍ ማን ናቸው?

    ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዋትኮፍ (ቀኝ)

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ጃሬድ ኩሽነር (ግራ) እና ስቲቭ ዋትኮፍ (ቀኝ)

    ስቲቭ ዊትኮፍ እና ጃሬድ ኩሽነር ከኢራን ጦርነት ጋር የተያያዘ ተጨማሪ ንግግር ለማድረግ ዛሬ ፓኪስታን እንደሚጓዙ ዋይት ሀውስ አስታውቋል። ሁለቱ የትራምፕ ተደራዳሪዎች ማናቸው? በሰላም ንግግሩ የሚሳተፉትስ ለምንድነው?

    ጃሬድ ኩሽነር የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አማች ሲሆኑ ባለቤታቸው የፕሬዝዳንቱ ልጅ ኢቫንካ ትራምፕ ናት።

    በትራምፕ የመጀመሪያው ሥልጣን ዘመን የፕሬዝዳንቱ አማካሪ ሆነው ሰርተዋል። አሁን ይህ አይነት ሹመት ባይኖራቸውም ቁልፍ ዓለም አቀፉ ጉዳዮች ላይ ይሳተፋሉ። እስራኤል እና ሐማስ የተኩስ አቁም ያደረጉበት ድርድር ላይም ተሳትፎ ነበራቸው።

    ስቲቭ ዊትኮፍ የሪል ስቴት አልሚ እና የትራምፕ ወዳጅ ናቸው። ባለፈው ዓመት ትራምፕ ሁለተኛ የሥልጣን ዘመናቸውን ሲጀምሩ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዩ መልዕክተኛ ሆነው ተሾመዋል።

    የትራምፕ አስተዳደር ለዓለም አቀፍ ድርድሮች የሚልካቸው ሰው የሆኑት ዊትኮፍ፤ በእስራኤል እና ሐማስ እንዲሁም ሩሲያ እና ዩክሬን ንግግሮች ላይ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል።

  3. ኢራን ለእስራኤል ይሰላል ያለችውን ተቃዋሚ በሞት ቀጣች

    የስቅላት ገመድ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን በአገሪቱ በተካሄደው ተቃውሞ ወቅት የእስራኤል የስለላ ድርጅትን “ተልዕኮ” ይዞ በመንቀሳቀስ የወነጀለችውን ግለሰብ በስቅላት መቅጣቷን ከእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያላቸው ፋርስ እና ታስኒም የዜና ወኪሎች ዘገቡ።

    ኢፍራን ኪአኒ የተባለው ግለሰብ ባለፈው ጥር በተካሄደው ተቃውሞ ወቅት “ውድመት እና ቃጠሎ” በማድረስ እንዲሁም “ሽብር በመፍጠር” መከሰሱን የታስኒም ዘገባ ያመለክታል።

    የአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የቅጣት ውሳኔው ካስተላለፈበት በኋላ ዛሬ ጠዋት መሰቀሉን የዜና ወኪሎቹ ዘግበዋል።

    እስራኤል በጉዳዩ ላይ አስተያየት አልሰጠችም።

    የኢራን ገንዘብ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ማሽቆልቆሉን እና የኑሮ ውድነት መናሩን ተከትሎ ባለፈው ታህሳስ ላይ የተቀሰቀው የኢራን ተቃውሞ በጥር ወር በመላ አገሪቱ ተስፋፍቶ ነበር።

    ተቃውሞ የወጡ ሰልፈኞች በኢራን ባለሥልጣናት ኃይል የተሞላት እርምጃ ተወስዶባቸዋል። የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሚናገሩት ተቃውሞውን ለማፈን በተወሰደው እርምጃ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል።

  4. የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፓኪስታን የሄዱት “ስለ ኒውክሌር ለመወያየት” አለመሆኑን የአገሪቱ ከፍተኛ ፖለቲከኛ ተናገሩ

    ኢብራሂም አዚዝ ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ ነበሩ

    የፎቶው ባለመብት, IRGC

    የምስሉ መግለጫ, ኢብራሂም አዚዝ ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ ነበሩ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ በፓኪስታን ጉዟቸው ወቅት “ከኒውክሌር ንግግር ጋር የተያያዘ ምንም ዓይነት ሥራ” እንደሌላቸው የአገሪቱ ብሔራዊ ደህንነት ኮሚቴ ኃላፊ ተናገሩ።

    ኢብራሂም አዚዝ ትናንት ምሽት ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ኢስላማባድ የሚገኙት “በሁለትዮሽ ግንኙነት ላይ ለመወያየት ብቻ” መሆን ተናግረዋል።

    ከዚህ በፊት የእስላማዊው አብዮታዊ ዘብ አዛዥ የነበሩት አዚዝ በኒውክሌር ላይ የሚደረግ ንግግር “ከኢራን ጠንካራ ቀይ መስመሮች መካከል አንዱ ሆኖ ይቆያል” ብለዋል።

    አሜሪካ ቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራሟን እንደታቆም የምትፈልግ ሲሆን ይህም የመጨረሻው የሰላም ስምምነት አካል መሆን እንዳለበት በአጽንኦት ትናገራለች።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትናንትው ዕለት ቴህራን የስምምነት ሃሳቦችን ማቅረቧን እና እንደሚመለከቱት ተናገረው ነበር

    ትራምፕ ለሮይተርስ የዜና ወኪል አርብ ዕለት እንደተናገሩት ኢራን “የስምምነት ሃሳቦችን አቅርባለች እናም እናየዋለን” ቢሉም የስምምነት ነጥቦቹ ምን እንደሆኑ እንደማያውቁ ተናግረዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት አክለውም ኢራን ከስምምነት ላይ መድረስ የሚያስችላትን መንገድ ለመፈተሽ እና ለመነጋገር እንዲሁም የአሜሪካን ፍላጎቶች የሚያሟላ የስምምነት ሃሳቦችን እያዘጋጀች ነው ብለዋል።

  5. ቱርክ ከአሜሪካ እና ኢራን የሰላም ስምምነት በኋላ ሆርሙዝን ከፈንጂ ማጽዳት ላይ ልትሰማራ እንደምትችል ገለጸች

    በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚቀዝፉ መርከቦች

    የፎቶው ባለመብት, REUTERS

    የቱርክ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃካን ፊዳን በቴህራን እና ዋሽንግተን ሊደረስ ከሚችል የሰላም ስምምነት በኋላ አገራቸው የሆርሙዝ ወሽመጥን ከፈንጂ የማጽዳት ሥራ ላይ መሳተፍ እንደምትችል አስታወቁ።

    ፊዳን አርብ ምሽት ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት ከማንኛውም ስምምነት በኋላ የቴክኒክ ቡድን በወሽመጡ የተጠመዱ ፈንጂዎችን ማምከን ሥራ ላይ ለመሠማራት እየጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል።

    አክለውም ቱርክ እንዲህ ዓይነት ጥረቶችን እንደ ሰብዓዊ ግዴታ እንደምትመለከተው ገልጸዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማንኛውም የፈንጂ የማምከን ሥራ የሚሠራው ከተለያዩ አገራት በተውጣጡ ቴክኒካል ቡድን መሆንን ገልጸው ከኢራን እና የአሜሪካ የሰላም ስምምነት በኋላ የሚመሠረት መሆኑን አስታውቀዋል።

    ቱርክ በእነዚህ ሁኔታዎች ውስጥ በፈንጂ ማምከን ሥራዎች ላይ በመሳተፍ ረገድ "ችግር የለባትም" ብለዋል።

    ፊዳን ወደፊት ከተለያዩ አገራት ተውጣጥቶ የሚመሰረተው የቴክኒክ ባለሙያዎች ጥምረት የአዲስ ግጭት አካል የሚሆን ከሆነ ቱርክ አቋሟን መልሳ እንደምትመለከት አስጠንቅቀዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ፊዳን ከኢራን የኒውክሌር መርሃ ግብር ጋር የተያያዙ ጉዳዮች በፓኪስታን በሚደረገው ቀጣይ ዙር ውይይት ሊፈቱ ይችላሉ ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል።

  6. የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ከፓኪስታን ጦር አዛዥ ጋር ተገናኙ

    ዛሬ ማለዳ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የፓኪስታኑ መከላከያ አዛዥ በኢዝላማባድ ተገናኝተው ተወያይተዋል

    የፎቶው ባለመብት, Iranian Ministry of Foreign Affairs

    የምስሉ መግለጫ, ዛሬ ማለዳ የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የፓኪስታኑ መከላከያ አዛዥ በኢዝላማባድ ተገናኝተው ተወያይተዋል

    ትናንት ምሽት ኢስላማባድ የደረሱት የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከፓኪስታኑ ጦር አዛዥ ፊልድ ማርሻል ጋር ተገናኝተው ተወያዩ።

    አራጋቺ ከፓኪስታን ባለሥልጣናት ጋር ከተወያዩ በኋላ ወደ ኦማን እና ሩሲያ እንደሚጓዙ አስታውቀዋል።

    በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባጋሩት ጽሑፍ “ከአጋሮቻችን ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ጋር ለመተባበር እና በቀጠናዊ ጉዳዮች” ላይ እንደሚወያዩ አስታወቀው ነበር።

    ምንም እንኳ ቴህራን በኢራን እና አሜሪካ መካከል የታቀደ ቀጥተኛ ንግግር የለም ብትልም የአሜሪካ ልዑካን ወደ ኢስላማባድ እንደሚጓዙ ይጠበቃል።

    ፓኪስታን በከተማዋ ያለውን የጸጥታ ሁኔታ እንዳጠናከረች ሲሆን እስካሁን ድረስ ግን በሁለቱ አገራት መካከል ስለሚደረግ ሁለተኛ ዙር የፊት ለፊት ውይይት የታወቀ ነገር የለም።

    ፓኪስታን በቴህራን እና በዋሺንግተን መካከል ሁለተኛው ዙር የሰላም ውይይት ይደረጋል ተብሎ ከታቀደበት ጊዜ አንስቶ የከተማዋን ጸጥታ አጠናክራለች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ፓኪስታን በቴህራን እና በዋሺንግተን መካከል ሁለተኛው ዙር የሰላም ውይይት ይደረጋል ተብሎ ከታቀደበት ጊዜ አንስቶ የከተማዋን ጸጥታ አጠናክራለች
  7. ስዊዘርላንድ “ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች” ለማገዝ ቴህራን ውስጥ የሚገኘው ኤምባሲዋን በድጋሚ ከፈተች

    ስዊዘርላንድ በኢራን ዋና ከተማ ቴህራን ውስጥ የሚገኘውን ኤምባሲዋን በሂደት በድጋሚ እየከፈተች መሆኑን የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    ኤምባሲው ኢራን ውስጥ የአሜሪካን ፍላጎቶች በመወከል እንደሚንቀሳቀስ ተነግሯል። አሜሪካ በአውሮፓውያኑ 1979 የኢራን አብዮት ፈንድቶ የኤምባሲ ሠራተኞቿ ታግተው ከተወሰዱ በኋላ ቴህራን ውስጥ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የሚወክላት ተቋም የላትም።

    የስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳስታወቀው ኤምባሲውን የመክፈት ውሳኔ የተላለፈው ከኢራን እና ከአሜሪካ ጋር ምክክር ከተደረገ በኋላ ነው። አውሮፓዊቷ አገር "ግጭትን ለማርገብ እና ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ለሚደረጉ ማናቸውም ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች" መስሪያ ቤቶቿን ለድጋፍ ለማዋል ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች።

  8. የእስራኤል ጦር እና ሄዝቦላህ የተኩስ አቁሙን በመጣስ እርስ በእርሳቸው ተካሰሱ

    ታንክ ላይ የቆሙ የእስራኤል ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል የተኩስ አቁም ስምምነት ለሦስት ሳምንታት መራዘሙን ይፋ ካደረጉ በኋላ ባሉት ቀናት የእስራኤል ጦር እና የሄዝቦላህ ታጣቂዎች የተኩስ አቁሙን በመጣስ ተካሰሱ።

    የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ሄዝቦላህ በደቡባዊ ሊባኖስ በሚገኙ ወታደሮቹ ላይ አጥፍቶ ጠፊ ድሮኖችን በመላክ ጥሰት መፈጸሙን አስታውቋል።

    “ይህ ክስተት የተኩስ አቁም ስምምነትን በግልጽ የሚጥስ ነው” ሲል የመከላከያ ሠራዊት አባላት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳልደረሰ ገልጿል።

    ሄዝቦላህ በበኩሉ እስራኤል "የተኩስ አቁም ስምምነቱን በመጣሷ" ምክንያት አርብ ዕለት ከሰዓት በኋላ እና ማታ የእስራኤልን ወታደሮች እና ድሮኖች ላይ አምስት ያህል ጥቃቶችን መሰንዘሩን አስታውቋል።

  9. አሜሪካ የኢራን ነዳጅ ንግድ ላይ አዲስ ማዕቀቦችን መጣሏን አስታወቀች

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት “የኢራንን ሕገ ወጥ የነዳጅ ንግድ ማስተጓጎል የሚያስችል ቆራጥ እርምጃ” እየወሰደ መሆኑን ገለጸ።

    የአገሪቱ ግምጃ ቤት የዚህ እርምጃ አካል የሆኑ አዲስ ማዕቀቦችን ኢራን ላይ ጥሏል። ማዕቀቡ የተጣለው “ዋና፣ እና ገለልተኛ የቻይና የነዳጅ ማጣሪያ” ላይ እንዲሁም “በሌሎች 40 ገደማ ዒላማዎች" ላይ እንደሆነ ተገልጿል።

    በግምጃ ቤቱ ድረ ገጽ ላይ የወጣው መረጃ እንደሚያሳየው ከቻይናው ነዳጅ ማጣሪያ በተጨማሪ ሌሎች 40 ገደማ የሚሆኑ ተቋማት እና የነዳጅ ጫኝ መርከቦችም ማዕቀብ ዝርዝሩ ውስጥ ተካትተዋል።

    አዲሶቹ ማዕቀቦች "ለኢራን የነዳጅ ኤክስፖርት ወሳኝ የሕይወት መስመሮች" እንደሆኑ ግምጃ ቤቱ ገልጿል።

    የግምጃ ቤት ኃላፊው ስኮት ቤሰንት በኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ አሜሪካ "[ከኢራን] አገዛዝ ጋር የተገናኙ ማናቸውንም የፋይናንስ መስመሮች ዒላማ ታደርጋለች" ብለዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘው ግምጃ ቤቱ 344 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ ዲጂታል ገንዘብ (ክሪፕቶከረንሲ) ማገዱን ገልጿል።

    የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱም በበኩሉ እነዚህ ማዕቀቦች የኢራን አገዛዝ "በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚያከናውናቸው ቀጣናዊ መረጋጋትን የሚያናጉ ተግባራት" የሚውሉ የገቢ ምንጮችን ያቋርጣሉ ብሏል።

  10. የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ለሰላም ንግግር ወደ ፓኪስታን ሊጓዙ ነው፤ ኢራን የታቀደ ቀጥተኛ ንግግር እንደሌለ ገልጻለች

    የትራምፕ አማች ጃሬድ ኩሽነት (በስተግራ) እና የፕሬዝዳንቱ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ (በስተቀኝ) ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ እንዲሚጓዙ ተገልጿል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የትራምፕ አማች ጃሬድ ኩሽነት (በስተግራ) እና የፕሬዝዳንቱ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ (በስተቀኝ) ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ እንዲሚጓዙ ተገልጿል

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ትናንት ምሽት ፓኪስታን የደረሱ ሲሆን የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደርም ሁለት ተደራዳሪዎቹን ወደ ዋና ከተማዋ ኢዝላማባድ እንደሚልክ ገልጿል።

    እንደ ዋይት ሐውስ ገለጻ የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ ስቲቭ ዊትኮፍ እና አማቻቸው ጃሬድ ኩሽነር ቅዳሜ ወደ ኢዝላማባድ የሚበርሩት ኢራን “በአካል” መነጋገር ስለፈለገች ነው።

    ንግግሩ ውጤታማ የሚሆን ከሆነ የተደራዳሪው ቡድን መሪ የሆኑት የአሜሪካ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ወደ ፓኪስታን ለመጓዝ “ዝግጁ” መሆናቸውን የዋይት ሐውስ ፕሬስ ኃላፊ ካሮሊን ሌቪት ተናግረዋል።

    በኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል የወጣው መረጃ ግን ከዚህ የተለየ ነው። ከኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጋር አርብ ምሽት ኢዝላማባድ መድረሳቸውን የገለጹት የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ቃል አቀባይ ኢስማኢል ባቃኢ፤ ሚኒስሩ “ከፓኪስታን ከፍተኛ አመራሮች ጋር” እንደሚነጋገሩ ገልጸዋል።

    አክለውም “በኢራን እና አሜሪካ መካከል እንዲካሄድ የታቀደ ስብሰባ የለም። የኢራን ምልከታዎች ለፓኪስታን ይቀርባሉ” ሲሉ የቴህራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ተደራዳሪዎች ጋር በቀጥታ እንደማይነጋገሩ አመልክተዋል።

    አርብ ዕለት ከጋዜጠኞች ጋር ቆይታ የነበራቸው የዋይት ሐውስ ቃል አቀባይ ሌቪት እንደተናገሩት ፕሬዝዳንት ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸውን ወደ ኢዝላማባድ የላኩት “ኢራናውያኑን ለመስማት” ነው። ትራምፕ “ሁሌም ለዲፕሎማሲ ዕድል ለመስጠት ፈቃደኛ” መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

    “በእርግጠኝነት ባለፉት ሁለት ቀናት ከኢራን ወገን በኩል የተወሰነ መሻሻል ተመልክተናል” ብለዋል።

    በኢዝላማባድ የሚገኘው የኢራን ኤምባሲ ግን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አራግቺ በፓኪስታን ጉዟቸው ያቀዱት “የሁለትዮሽ ጉዳዮችን ለመገምገም” እና ቀጣናዊ ሁኔታዎችን ለመወያየት እንደሆነ ገልጿል። አራግቺ ከፓኪስታን በተጨማሪ ወደ ኦማን እና ሩሲያ እንደሚጓዙ አስታውቀዋል።

    ከዚህ አስቀድሞ አሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትርምፕ ባለሥልጣናቶቻቸው ኢራን ውስጥ “አሁን ኃላፊነት ላይ ካሉት ሰዎች ጋር” እየተደራደሩ መሆኑን ተናግረው ነበር።

    ኢራን “መደራደሪያ አቅርባለች፤ እንመለከተዋለን” ብለዋል፤ ቀርቧል ስላሉት የድርድር ነጥቦች ግን ዝርዝር መረጃ ሳይሰጡ ቀርተዋል።

  11. የአውሮፓ ሕብረት፤ ስምምነት ላይ የሚደረስ ከሆነ ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን ለመቀነስ ክፍት መሆኑ ተገለጸ

    የአውሮፓ መሪዎች

    የፎቶው ባለመብት, EPA/Shutterstock

    የአውሮፓ ሕብረት መሪዎች ዛሬ ከግብጽ፣ ሶርያ እና ሊባኖስ መሪዎች ጋር ቆጵሮስ ውስጥ ስብሰባ አካሂደዋል።

    የጀርመን ቻንስለን ፍሬድሪክ መርዝ ሁሉን አቀፍ ስምምነት ላይ የሚደረስ ከሆነ የአውሮፓ ህብረት ኢራን ላይ የተጣሉ ማዕቀቦችን በሂደት ለመቀነስ ፍቃደኛ መሆኑን ለአገራቱ መሪዎች መናገራቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የጀርመኑ መሪ “ይህንን ሂደት ለማገዝ ማድረግ ከምንችለው አስተዋፆ አንዱ ነው፤ ወደ ዘላቂ ተኩስ አቁም ይመራል የሚል ተስፋ አለን” ሲሉ ተናግረዋል።

    የአውሮፓ ሕብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አንቶኒዮ ኮስታ በበኩላቸው የሆርሙዝ ወሽመጥ “ያለምንም እገዳ እና ያለ ምንም ክፍያ በአፋጣኝ መከፈት አለበት” ማለታቸውን ኤኤፍፒ የዜና ወኪል ዘግቧል። የባሕር መተላለፊያው “ለመላው ዓለም ወሳኝ” መሆኑንም ጠቅሰዋል።

    ስብሰባው ከመጀመሩ አስቀድሞ አስተያየት የሰጡት የሕብረቱ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ ካጃ ካላስ በበኩላቸው ከኢራን ጋር የሚደረገው ንግግር በአውሮፓውያኑ 2015 የተደረሰው የኢራን የኒውክሌር ስምምነት አይነት ውጤት የማያስገኝ ከሆነ መላው ዓለም የበለጠ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

    ከ10 ዓመት በፊት የተፈረመው የኒውክሌር ስምምነት የፈረሰው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በመጀመሪያው የሥልጣን ዘመናቸው አሜሪካን ከውሉ ፈራሚነት ካስወጡ በኋላ ነበር።

  12. የኢራን አምባሳደር አሜሪካ በቀጣይ ድርድሮች ተጨባጭ አቋም መያዝ አለባት አሉ

    የኢራን አምባሳደር ሆኑት አሊ ባህሬኒ

    ጄኔቫ ውስጥ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢራን አምባሳደር ሆኑት አሊ ባህሬኒ በቴህራን እና ዋሽንግተን መካከል የሚደረጉ ድርድሮች እንዲቀጥሉ የሚፈለግ ከሆነ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የጣለችውን እገዳ ማብቃት እንዳለበት ተናገሩ።

    ከቢቢሲ ጋር ቃለ መጠይቅ ያደረጉት አምባሳደሩ፤ አሜሪካ ጣለችው እገዳ “ከፍተኛ” የተኩስ አቁም “ጥሰት” መሆኑን ገልጸዋል።

    በድጋሚ ድርድር ውስጥ በሚገባበት ወቅት “አሜሪካ ለኢራን መብቶች እና ለኢራን ምክንያታዊ ጥያቄዎች እውቅና በመስጠት ተጨባጭ አካሄድ ልትከተል” እንደሚገባ ተናግረዋል።

    ቴህራን ድርድር የምታደርገው “ሌላኛው ወገን ኢራንን ለማጥቃት ተጨማሪ ዝግጅት” የሚያደርግበት ዕድል ለመስጠት እንዳልሆነም አክለዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ወታደሮች ትዕዛዝ የሚሰጣቸው ከሆነ በድጋሚ ዘመቻ ለመክፈት ዝግጁ መሆናቸውን ከዚህ ቀደም ተናግረው ነበር።

    አምባሳደሩ ከቢቢሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ ቀጣይ እርምጃ ምን መሆን አለበት የሚለውን በተመለከተ በኢራን ከፍተኛ አመራሮች መካከል ክፍፍል ተፈጥሯል መባሉን ውድቅ አድርገዋል። ይልቁንም ችግር የሆነችው “ሙሉ ተቃርኖ” እና ክፍፍል ውስጥ ያለችው አሜሪካ መሆኗን ተናግረዋል።

  13. የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ፈንጂ ማጥመድ “የተኩስ አቁም ጥሰት” ነው አሉ

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት ኢራን በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ ፈንጂ ለማጥመድ የምትሞክር ከሆነ “እንደ የተኩስ አቁም ስምምነት ጥሰት” እንደሚቆጠር እና በዚያው አግባብ ምላሽ እንደሚሰጠው ተናገሩ።

    መከላከያ ሚኒስትሩ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረጉ ጉዞዎች ላይ የጣለችውን እገዳ “ያለ ማመንታት እና ይቅርታ” እያስፈጸመች መሆኑን ገልጸዋል። አሜሪካ እስከ ዛሬ ጠዋት ድረስ በአጠቃላይ 34 መርከቦችን ማስመለሷንም ጠቅሰዋል።

    ያለ አሜሪካ ፈቃድ የትኛውም መርከብ በወሽመጡ አያልፍም ሲሉ የተናገሩት ሄግሴት “ተጨማሪ [መርከቦችን] እንይዛለን” ብለዋል።

    ዋሽንግተን ይህንን እገዳ የጣለችው ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚደረግ ጉዞን ከልክላ ከአንድ ወር በላይ ከቆየች በኋላ ነው። ኢራን ባለፉት ቀናት ሁለት መርከቦች ላይ ተኩስ እንደከፈተች እና እንደያዘች ተገልጾ ነበር።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ሄግሴት የተያዙት የአሜሪካ እና እስራኤል መርከቦች አለመሆናቸውን ተናግረዋል። አክለውም “ፈጣን ጀልባ ከሽጉጥ እና የተሳሳተ ዓላማ ጋር የያዘ ሰው በሙሉ ሊያደርገው ይችላል” ሲሉ የኢራንን እርምጃ አጣጥለዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ባሕር ኃይል በውሃ መተላለፊያው ላይ ፈንጂ ለማጥመድ ወይም የመርከቦችን ጉዞ ለማስተጓጎል የሚሞክሩ የኢራን ፈጣን ጀልባዎችን እንዲያወድም ትዕዛዝ ሰጥተዋል። የመከላከያ ሚኒስትሩ ሄግሴትም “ያለ ምንም ማመንታት ለማውደም እንተኩሳለን” ብለዋል።

    መከላከያ ሚኒስትሩ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ፈንጂ እንደምታጠምድ ስለመዛቷም ተጠይቀዋል። “በግድ የለሽነት እና ኃላፊነት በጎደለው መንገድ ተጨማሪ ፈንጂዎችን ለማጥመድ የሚደረግ ሙከራ ካለ ምላሽ እንሰጠዋለን። የተኩስ አቁም ጥሰት ነው” ብለዋል።

    ኢራን አሁንም ቢሆን “ጥሩ እና ብልህ ስምምነት” ላይ ለመድረስ ዕድል እንዳላት ተናግረዋል። ኢራናውያን “በብልህነት ለመምረጥ መስኮቱ ክፍት እንደሆነ ያውቃሉ” ያሉት ሄግሴት፤ ማድረግ ያለባቸው “ትርጉም ባለው እና ሊረጋገጥ በሚቻል መልኩ የኒውክሌር መሣሪያን መተው” ብቻ እንደሆነ ገልጸዋል።

  14. የኢራን ልዑክ ዛሬ ለንግግር ወደ ፓኪስታን ይጓዛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ምንጮች ለቢቢሲ ተናገሩ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የኢራን ተደራዳሪ ልዑክን ከሚመሩት አንዱ የሆኑት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራግቺ ዛሬ ማታ ኢስላማባድ ይደርሳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የፓኪስታን መንግሥት ምንጮች ለቢቢሲ ተናገሩ።

    የዜና ወኪሉ ሮይተርስ በበኩሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የሚጓዙት አነስተኛ ቁጥር ያለው አባላትን የያዘ ቡድን አስከትለው እንደሆነ እና ከአሜሪካ ጋር የሚደረግ ንግግር ላይ ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ዘግቧል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጉዞ የተሰማው ዛሬ ከፓኪስታን ባለሥልጣናት ጋር ንግግር ማድረጋቸውን ከገለጹ በኋላ ነው።

    ከፓኪስታን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እንዲሁም የአገሪቱ ጦር ኃይሎች አዛዥ ጋር በነበራቸው ንግግር ከአሜሪካ ጋር ስለሚደረገው ግጭት ተወያይተዋል።

    በንግግራቸው ወቅት “ከተኩስ አቁም ጋር ተያያዙ ጉዳዮች” እንደተነሱ የተገለጸ ሲሆን ተኩስ አቁሙ ግን በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ስላለው ይሁን በሊባኖስ እና እስራኤል መካከል ስለተፈጸመው በግልጽ አልተጠቀሰም።

    አሜሪካ እና ኢራን ሁለተኛ ዙር ንግግር የማድረጋቸው ጉዳይ እስካሁን ማረጋገጫ ባይሰጥበትም በአሸማጋይነት እየሰራች ያለችው ፓኪስታን ግን ድርድሩን ለማስተናገድ ዝግጁ ሆና ቀጥላለች።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወደ ፓኪስታን ያደርጉታል ተባለውን ጉዞ በተመለከተ ከኢራንም ሆነ ከአሜሪካ በኩል ይፋዊ ማረጋገጫ አልተሰጠም።

  15. እስራኤላውያን በጥርጣሬ የሚመለከቱት የተኩስ አቁም ስምምነት

    ሊባኖስ ድንበር ላይ የተሰማሩ የእስራኤል ወታደሮች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በሊባኖስ እንደታየው በሁለትዮሽ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ዙሪያ እስራኤል ውስጥ የጎላ ክፍፍል የለም። ምን ያህል ውጤታማ ይሆናል በሚለው ላይ ግን ብዙ ጥርጣሬ አለ።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ የእስራኤል-ሊባኖስ የተኩስ አቁም ስምምነት መራዘሙን ከማወጃቸው በፊት፣ ሄዝቦላህ በሰሜናዊ እስራኤል የድንበር ከተማ ነዋሪዎች ላይ የሮኬት ጥቃት ፈጽሟል።

    በርግጥ ያስወነጨፋቸው ሮኬቶች ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሱም።

    በሰሜን አካባቢ የሚኖሩ እስራኤላውያን አሁንም በአደጋ እና እርግጠኛ ባለመሆን ውስጥ እየኖሩ እንደሆነ በመናገር ለጊዜው መደበኛ ሕይወታቸውን ማቆማቸውን ተናግረዋል።

    “ስለተኩስ አቁም ስምምነት ከፍተኛ ጥርጣሬ አለን” ሲሉ የኪርያት ሽሞና የቀድሞ ምክትል ከንቲባ ገልጸዋል።

    “አልፎ አልፎ የሚሰነዘሩ ጥቃቶች መደበኛ እንዲሆኑ ፈቃደኛ አንሆንም” ብለዋል።

    በካፋር ጊላዲ ነዋሪ የሆኑት ኒሳን ዜቪ ደግሞ “ይህ የይስሙላ እንቅስቃሴ ብቻ በመሆኑ ነዋሪዎቹ ከፍተኛ ስጋት አላቸው፣ ሄዝቦላህ ራሱን እያስታጠቀ፣ ሊባኖስን ለመቆጣጠር እና እስራኤልን ለመጉዳት ያለውን ፍላጎት እንደገና እያደራጀ እና እየቀጠለበት” ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    እስራኤል ከሊባኖስ ጋር በምትዋሰንበት የሜቱላ ድንበር አቅራቢያ የሚኖሩት ሊያት ኮሄን ራቪቭ በበኩላቸው “እዚህ ጦርነት የሚፈልግ ማንም የለም” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    “የተኩስ አቁም ስምምነቱ በደህንነት እውነታ ላይ ለውጥ በማምጣት ስጋቱን በትክክል ማስወገድ እና የተለመደው ሕይወት ሲያስቀጥል ካላሳየ መፍትሄ አይሆንም። መዘግየት ብቻ ነው” ብለዋል።

  16. ኢራን እና ፓኪስታን “ከተኩስ አቁሙ ጋር በተያያዘ” ተወያዩ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራጋቺ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከፓኪስታን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር በግጭቱ ዙሪያ መነጋገራቸው ተሰማ።

    አባስ አራጋቺ በቴሌግራም ላይ ባጋሩት መግለጫ ከፓኪስታን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢሻቅ ዳር እንዲሁም ከመከላከያ አዛዡ ፊልድ ማርሻል አሲም ሙኒር ጋር መወያየታቸውን ጠቅሰዋል።

    በንግግራቸው “በቀጠናዊ ሁኔታዎች እና በተኩስ አቁሙ ዙሪያ” መነጋገራቸውን ገልጸዋል።

    አራጋቺ ከፓኪስታን ባለሥልጣናት ጋር በነበራቸው ውይይት ያነሱት ከአሜሪካ ጋር ስላላቸው የተኩስ አቁም ይሁን ወይም እስራኤል እና ሊባኖስ ስለደረሱበት ስምምነት ያሉት ነገር የለም።

    የፓኪስታን ዋና ከተማ ኢዝላማባድ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ሊደረግ ለሚችል ሁለተኛ ዙር የሰላም ውይይት ዝግጁ ሆና እየጠበቀች ቢሆንም መቼ እንደሚካሄድ እስካሁን ድረስ የታወቀ ነገረ የለም።

  17. የኢራን አመራሮች አንድነታቸውን የሚያሳይ መልዕክት አስተላለፉ

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት እና ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images/Mizan

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን አዳዲሶቹን መሪዎች “በሁከት” እና “በከባድ ሁኔታ የተከፋፈሉ ” ናቸው በማለት በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ገልጸዋል።

    ቴህራን ደግሞ እኩለ ሌሊት ካለፈ በኋላ ለሁሉም የኢራን የሞባይል ተጠቃሚዎች የጽሑፍ መልዕክት አስተላልፋለች።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ “ልዩነትን ለመዝራት” ላደረጉት ጥረት ምላሽ ለመስጠት ከፕሬዝዳንቱ፣ ከፓርላማ አፈ ጉባኤው፣ ከፍትህ ሚኒስትሩ እና ከሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናት የተላከ “የጋራ መልእክት” ነው ተብሏል።

    “ኢራን ውስጥ አክራሪ ወይም ለዘብተኛ የሚባል ነገር የለም” ይላል መልዕክቱ። “ሁላችንም ኢራናውያን እና አብዮታዊ ነን… አንድ አገር፣ አንድ ሃሳብ” ይላል።

    ባለፈው ሳምንት በኢራን ሚዲያዎች ላይ በአንዳንድ ጥቃቅን ስልታዊ ጉዳዮች የአለመግባባት ምልክቶች በኢስላማዊ አብዮታዊ ጥበቃ ዘብ ጨምሮ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በተገናኘ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኅን ላይ ታይቷል።

    መልዕክቱ ከአሜሪካ ጋር በሚደረጉ ድርድሮች ውስጥ አስፈላጊ በሆኑ ዋና ዋና ውሳኔዎች ላይ መግባባት እንደሚሰፍን ለማሳየት የታሰበ ነው።

    ይህም የኢራንን ጉዳይ በርቀት ለሚከታተሉ ለሳምንታት በጦርነት እና በከፍተኛ የሃይማኖት መሪዎች እና አዛዦች ግድያ ምክንያት ስለመጣው ስርዓት የሚጋሩት ሃሳብ ነው።

    አሁን ብዙ ውሳኔ ሰጪዎች አሉ። አንዳንዶቹ የበለጠ ተራማጅ ሲሆኑ ሌሎች ደግሞ የበለጠ አክራሪ እንደሆኑ ተደርገው ይታያሉ።

    ሆኖም ሁሉም ከኒውክሌር ፕሮግራሙ እስከ ሆርሙዝ ወሽመጥ ድረስ ባሉ ጉዳዮች ላይ ያላቸው ቀይ መስመር ግልጽ ነው።

  18. የአውሮፓ ኅብረት በኢራን የሰላም ውይይት ውስጥ የኒውክሌር ባለሙያዎች እንዲሳተፉ ጠየቀ

    የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ

    የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ኃላፊ የኒውክሌር ባለሙያዎች በኢራን የሰላም ድርድር ውስጥ ካልተሳተፉ ከቴህራን የሚሰነዘሩ ማስፈራሪያዎች "የበለጠ አደገኛ" ሊሆኑ እንደሚችሉ ተናገሩ።

    ካጃ ካላስ በቆጵሮስ የአውሮፓ ኅብረት መሪዎች ጉባዔ ላይ ባደረጉት ንግግር ማንኛውም ስምምነት ከዚህ በፊት ከተደረጉት ደካማ የመሆን አደጋ አለው ብለዋል።

    ኢራን ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ አገራት ጋር እአአ በ2015 የተፈራረመችው ስምምነትን የተቃወሙት ትራምፕ አገራቸውን ማስወጣታቸው ይታወሳል።

    በዚህ ስምምነት መሠረት ኢራን ሚስጥራዊ የሆኑ የኒውክሌር እንቅስቃሴዎቿን ለመገደብ እና ዓለም አቀፍ ተቆጣጣሪዎች ወደ ቴህራን እንዲገቡ በመፍቀድ በምላሹ የተጣሉባት የኢኮኖሚ ማዕቀቦቹ እንዲነሱ ተስማምታለች።

    "ውይይቱ ስለ ኒውክሌር (ፕሮግራሙ) ብቻ ከሆነ እና በጠረጴዛው ዙሪያ የኒውክሌር ባለሙያዎች ከሌሉ፣ ከቀደመው ጋር ሲነጻጸር ደካማ የሆነ ስምምነት ላይ እንደርሳለን" ሲሉ ካላስ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

    “እናም በቀጣናው ውስጥ ያሉት ችግሮች፣ የሚሳዔል ፕሮግራሞች፣ ድጋፍ ስለምትሰጣቸው ታጣቂዎች፣ እንዲሁም በአውሮፓ ውስጥ ያሉ የበይነ መረብ እንቅስቃሴዎች ካልተፈቱ፣ የበለጠ አደገኛ የሆነች ኢራን ትሆናለች” ሲሉ ተናግረዋል።

  19. የተኩስ አቁም የሊባኖስ መንግሥት ጥያቄ እንደነበር የአገሪቱ ማስታወቂያ ሚኒስትር ገለጹ

    የሊባኖስ ማስታወቂያ ሚኒስትር ፖል ሞርኮሰ

    የፎቶው ባለመብት, LIbanos Information Minister

    አንድ የሊባኖስ ከፍተኛ ባለሥልጣን መንግሥት የአገሪቱን ጦር በማሰማራት ሄዝቦላህን ትጥቅ ለማስፈታት “ወሳኝ እርምጃዎች” ሊወስድ እንደሚችል ገለፁ።

    ነገር ግን ይህንን ለማድረግ የእስራኤል ጦር ከሊባኖስ ጠቅልሎ መውጣት ይኖርበታል ብለዋል።

    የአገሪቱ ማስታወቂያ ሚኒስትር ፖል ሞርኮሰ ለቢቢሲ ኒውስዴይ የተኩስ አቁሙ ለሦስት ሳምንታት እንዲራዘም መንግሥታቸው ጠይቆ እንደነበር ተናግረዋል።

    ከተኩስ አቁሙ ባሻገር “እስራኤል በሊባኖስ ላይ በአየር፣ በባሕር ወይም በእግረኛ ጦሯ የምትፈጽማቸው ጥቃቶች እንዲቆም” የሚል እንደነበረበት አስረድተዋል።

    በተኩስ አቁም ስምምነቱ መሠረት ቤይሩት የሄዝቦላህ እና “ሌሎች ከመንግሥት ውጪ የሆኑ ታጣቂዎች” በእስራኤል ዒላማዎች ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ለመከላከል “ተጨባጭ እርምጃ” መውሰድ አለባት።

    ሞርኮስ የሊባኖስ መንግሥት የአገሪቱን ጦር በማሰማራት እና ወታደሮች “በሊባኖስ የመሣሪያ የበላይነት እንዲኖረው ለማድረግ”፤ “ተጨባጭ እርምጃዎችን” መውሰዱን ተናግረዋል።

    ነገር ግን መንግሥት ይህ ጦርነት ከመጀመሩ በፊት መውሰድ የጀመራቸው እርምጃዎችን የእስራኤል “ወረራ” እና “ጥቃቶች”፤ “ባሉ ለውጦች ላይ እንቅፋት” መሆናቸውን አብራርተዋል።

    አክለውም “እነዚያን ተጨባጭ እርምጃዎች ሠራዊቱን ወደ ድንበር በማሰማራት ዳግም ለመጀመር ፈቃደኞች ነን” ብለዋል።

  20. ትራምፕ ኢራን ላይ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ እንደማይጠቀሙ ተናገሩ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አሜሪካ በመደበኛ ሁኔታ ወታደራዊ ዓላማዎቿን አሳክታለች ያሉት ትራምፕ ኢራን ላይ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ እንደማይጠቀሙ ተናገሩ።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት የኒውክሌር ጦር መሣሪያ ይጠቀሙ እንደሆን ከጋጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ለምን እፈልገዋለሁ” በማለት ጥያቄውን “የማይረባ” ብለውታል።

    አክለውም “እኛ ያለ ኒውክሌር ጦር መሣሪያን ሙሉ በሙሉ ካጠፋናቸው ለምን እጠቀማለሁ?” ሲሉ ጠይቀዋል።

    "የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ማንም ሰው እንዲጠቀምበት ፈጽሞ መፍቀድ የለበትም።"