ከአሜሪካ ጋር የሚኖረው “የጨዋታው ሕግ ተቀይሯል፤ የተመጣጠነ ምላሽ ዘመን አብቅቷል” - ኢራን

የፎቶው ባለመብት, Tabnak
ኢራን ከአሜሪካ በኩል ለሚሰነዘርባት ጥቃት የምትሰጠው ተመጣጣኝ የአጸፋ ምላሽ ማብቃቱን እና ለሚፈጸምባት ጥቃት የምትሰጠው ምላሽ ከባድ እንደሚሆን በኢራን መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ባለሥልጣን የሆኑት መሐመድ ባገር ጋሊባፍ ተናገሩ።
የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ እና ዋነኛ ተደራዳሪ ጋሊባፍ ፓርላማ ውስጥ ሲናገሩ፣ በአገራቸው ላይ ለሚፈጸም ጥቃት “የተመጣጠነ ምላሽ ዘመን እንዳበቃ እና የጨዋታው ሕግ እንደተቀየረ” ገልጸዋል።
መሐመድ ባገር ጋሊባፍ ባደረጉት ንግግር፣ ኢራን “ከጠቃላይ የከሐዲያን ግንባር" ጋር ሁሉን አቀፍ ጦርነት ውስጥ ናት ብለዋል።
ጨምረውም “ወታደራዊ ኃይሎቻችን በአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ በፈጸሙት ከባድ ጥቃቶች፣ የጠላት መሪዎች ተስፋ በመቁረጥ ውስጥ ገብተዋል፤ ከንቱ ቃላት እና መፈክሮችን በመጠቀም በጦር ሜዳ የተፈጠሩ መስለው የሚታዩ ፎቶዎችን እና ቪዲዮዎችን በሰው ሰራሽ አስተውሎት እያመረቱ ነው" ሲሉ ከስሰዋል።
ከአሜሪካ ጋር በሚደረገው ድርድር የኢራን ዋና ተወካይ የሆኑት ጋሊባፍ፣ “አሁን አሜሪካውያን የተመጣጠነ ምላሽ ዘመን እንዳበቃ ሊረዱ ይገባል። በቅርቡ በጠላት ጦር ሰፈር ላይ ባካሄድነው ዘመቻ የፈጸምናቸው ጥቃቶች የመጀመሪያዎቹ እርምጃዎች ብቻ ናቸው” ብለዋል።
"እስካሁን ካልተረዱ፣ ከመዘግየቱ በፊት ሊገነዘቡ ይገባል፤ የጨዋታው ሕግ ተቀይሯል። ከአሁን በኋላ በኢራን ጥቅም እና ደኅንነት ላይ የሚደረግ ማንኛውም ጥሰት ፈጣን፣ ከባድ እና የበለጠ አውዳሚ ምላሽ ያስከትላል" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።




















